

ከረጅም ጊዜ በፊት በብርቃ መንደር ክንዴ የሚባል ሰው ይኖር ነበር፡፡ ሥጋ መብላትም በጣም ይወድ ነበር፡፡
አንድ ቀን የብርቃ መንደር አለቃ ሁሉንም መንደርተኞች በወንድ ልጁ ሠርግ ላይ እንዲገኙ ጋበዛቸው፡፡
ክንዴ ደግሞ በሌላ እንቧይባድ በተባለች መንደርም ሌላ ድግስ እንዳለ ሰማ፡፡ ''አሃ! ሁለት ድግስ በአንድ ቀን!'' ሲል አሰበ ክንዴ፡፡
''ሁለቱንም ድግሶች መብላት አለብኝ፣'' አለ ክንዴ፡፡ መጀመሪያ ወደ እንቧይባድ እሄድና ከዚያ ወደ ብርቃ ተመልሼ እመጣለሁ፡፡.
ክንዴ በጠዋት ተነስቶ ወደ እንቧይባድ ሄደ፡፡ ዘወር ዘወር ብሎ ሲያይ ድግሱ ገና እንዳልጀመረ ተረዳ፡፡ ''ወደ ብርቃ እመለስና ወደ እንቧይባድ ደግሞ በኋላ ላይ እመለሳለሁ'' በማለት ወሰነ፡፡
ክንዴ ወደ ብርቃ ሥጋው ተዘጋጅቶ ይጠብቀኛል ብሎ አስቦ ለመብላት ሄደ፡፡በዚህ ወቅት በጣም ርቦት ነበር፡፡ ሲደርስ ወንዶቹና ሴቶቹ ምግቡን ገና እያዘገጃጁ ነበር፡፡
''እንቧይባድ ላይ ወጥ ሰሪዎቹ ለመስራት ሲዘገጃጁ ነበር ወደዚህ የመጣሁት'' በማለት አሰበ፡፡ ''ምግቡ አሁን ደርሶ ይሆናል'' ብሎ ክንዴ ወደ እንቧይባድ ለመመለስ ወሰነ፡፡.
ክንዴ እንቧይባዱ ድግስ ጋ ሲደርስ ሰዎቹ በልተው ጨርሰዋል፡፡ እንግዶች ለሙሽሪትና ለሙሽራው ስጦታ እየሰጡ ነበር፡፡ ክንዴ በጣም ስስታም ነበር፡፡ የሚሰጠው ስጦታ አልነበረውም፡፡ መብላት ብቻ ነበር የፈለገው፡፡
ክንዴ ምግቡን በማጣቱ በጣም ተበሳጭቶ ነበር፡፡ ወደ ብርቃ መንደር ለመመለስ ወሰነ፡፡ ስለተራበና ስለደከመው በፍጥነት ሊጓዝ አልቻለም ነበር፡፡
ብርቃ ሰዎቹ ሲጨፍሩና ሲዘፍኑ ደረሰ፡፡ ምግቡን ሁሉ በልተው ጨርሰው ነበር፡፡
ምግብ ምንም እንዳልቀረ ሲሰማ ክንዴ ወድቆ ራሱን ሳተ፡፡ የሁለቱም ድግስ ስጋ አምልጦት ነበር፡፡ ያገኛት በትንሽ ስኒ የነበረች ገንፎ ብቻ ነበረች፡፡
ተናዶና ተርቦ ቀስ ብሎ ወደ ቤቱ እያዘገመ ሄደ፡፡

